Monday, May 13, 2019

ልመናዋ ክብሯ በእኛ ለዘላለም ይደርብንና አምላክን የወለደች ክብርት እመቤታችን ያደረገችው ተአምር ይህ ነው
ልመናዋ ክብሯ በእኛ ለዘላለም በእውነት ይደርብንና አምላክን የወለደች በድንጋሌ ሥጋ በድንጋሌ ነፍስ የጸናች ክብርት እመቤታችን ያደረገችው ተአምር ይህ ነው፡- ለነቢያት ለሐዋርያት ለጻድቃንና ለሰማዕታት ሁሉ እመቤታቸው ድንግል ማርያም ናት፡፡ ምንም እንኳን ከአምላካቸው ዘንድ ለእነዚህ ሁሉ የድኅነት ቃል ኪዳን ቢሰጣቸውም የቃል ኪዳኑ መመኪያ አክሊል እናታችን ድንግል ማርያም ናት፡፡ ይህን የእርሷ ቃል ኪዳን በመስማት አምነው አምላክን የወለደች የእመቤታችንን ስም በመጥራት የዳኑትን ምን ያህል እንነግራችኋለን! በላዔ ሰብእ ትክክለኛውና የቀድሞ ስሙ ስምዖን ይባላል፡፡ አስቀድሞ ቅምር በሚባል አገር የሚኖር እጅግ ባለጸጋ ሰው ነበር፡፡ እንደ አብርሃም እንግዶችን እየተቀበለ ድኆችን እየመገበ የሚኖር ጻድቅ ነበር፡፡ የበጎ ነገር ሁሉ ጠላት ሰይጣን በዚህ ሥራው ቀናበትና ሊፈትነው በሦስት አረጋዊ ሽማግሌዎች ተመስሎ ‹‹ሥላሴ ነን›› ብሎ እንደ አብርሃም እንደተገለጠለት ሆኖ ተገለጠለት፡፡ ‹‹ሰይጣን ራሱ የብርሃን መልአክ እንዲመስል ራሱን ይለውጣል›› እንዳለ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ፡፡ 2ኛ ቆሮ 11፡14፡፡